የኢትዮጵያ ሠላም አስከባሪ በሱዳን ጥያቄ ከአቢዬ ሊወጣ ነው
ከፍተኛ ቁጥር ያለው የኢትዮጵያ ሠላም አስከባሪ በሱዳን ጥያቄ ከአቢዬ ግዛት ሊወጣ ነው
አቢዬ ግዛት በተባባሩት መንግሥታት ጥላ ስር በሰላም አስከባሪነት ተሰማርተው የሚገኙ ኢትዮጵያውያ ወታደሮችን ለማስወጣት የሱዳን መንግሥት እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጋር ከስምምነት መድረሳቸው ተዘገበ።
የሱዳን መንግሥት የዜና ወኪል የሆነው ሱና እንደዘገበው የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማሪያም አል-ሳዲቅ አል-መሐዲ ከተባበሩት መንግሥታት ባለስልጣናት ጋር ውይይት ካደረጉ በኋላ የኢትዮጵያ ወታደሮች በቀጣይ ሦስት ወራት ከአቢዬ እንዲወጡ እንደሚደረግ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በትግራይ የተከሰተውን ጦርነት ተከትሎ ሠራዊቷን ከሱዳን ድንበር ማንቀሳቀሷን ተከትሎ ሱዳን በኢትዮጵያ ቁጥጥር ስር የነበሩ ቦታዎችን ከያዘች በኋላ በሁለቱ አገራት መካከል አለምግባባት መከሰቱ ይታወሳል።
ይህንንም ተከትሎ ከወራት በፊት የሱዳን የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት "የኢትዮጵያ ሠራዊት በምሥራቃዊ የሱዳን ድንበር አካባቢ እየተጠናከረ ባለበት ጊዜ ስትራተጂክ በሆነው የሱዳን ማዕከላዊ ስፍራ ላይ የኢትዮጵያ ኃይሎች እንዲኖሩ መፍቀድ ምክንያታዊ አይሆንም" በማለት የመንግሥታቱ ድርጅት በስሩ ያሉትን የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ወታደሮችን እንዲያስወጣ ጥያቄ አቅርቦ ነበር።
ምንም አስተያየቶች የሉም